Wednesday, May 1, 2013

ብሂለ አበዉ ስለ ነገረ ህማማት


በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን
                    ብሂለ አበዉ ስለ ነገረ ህማማት
‹‹እጆቹን እግሮቹን በተቸነከረባቸዉ ችንካሮች መወጋቱን እናምናለን ነቢዩ  ኢሳይያስ እርሱ ደዌያችንን ወስዶ ህማማችን ተሸከመ እንዳለ››ቅዱስ ጎርጎርዮስ ሊቀ ጳጳስ
‹‹ነፍሱን ከስጋዉ በለየ ጊዜ በሲኦል ፈጥኖ ብርሃን ታየ ጌታችን በአካለ ስጋ ሳይሆን በ አካለ ነፍስ ወደ ሲኦል ሄደ ሲኦልም ተናወጠች መሰረቶቿም እፈርስ እፈርስ አሉ››ቅዱስ አትናቴዎስ ዘ እስክንድርያ
‹‹የሚሰዋ በግ እርሱ ነዉ የሚሰዋ ካህን እርሱ ነዉ፡፡ከባሕርይ አባቱ ከ አብ ከባሕርይ ህይወቱ ከመንፈስ ቅዱስ ጋርም መስዋዕት የሚቀበል እርሱ ነዉ፡፡››ያዕቆብ ዘ ስሩግ
‹‹ኃጢአታችን ለማሰተሰርይ በስጋ እንደታመመ እንደሞተ ከነፍሱም በተለየ ጊዜ ስጋዉን እንደገነዙ እናምናለን››የ ኢየሩሳሌም ኤጲስ ቆጶስ ቅ/ዮሐንስ
‹‹ምትሐት ያይደለ በእዉነት ተራበ ተጠማ ዳግመኛም ከኃጥአን ጋር በላ ጠጣ››ቅ/ባስልዮስ ዘ ቂሳርያ
‹‹ከ አብ ጋር አንድ እንደመሆንህ ሞት የሌለብህ አንተ ነህ ከእኛም ጋር አንድ እንደመሆንህ በፈቃድህ የሞትክ አንተ ነህ››ቅ/ኤራቅሊስ
                            ይኼን ያዉቁ ኑሯል
በሰሙነ ህማማት ከሰኞ እስከ ቅዳሜ የተከናወኑት ተግባራት እንመልከት
ሰኞ፡-ጌታችን ከቢታንያ ሲወጣ ተራበ ቅጠል ያለባትን በለስ ከሩቁ አይቶ በለሲቱን ቀረባት ነገር ግን ከቅጠል በቀር ምንም አልተገኘባትም ከአሁን ጀምሮ ማንም ከ አንች ፍሬን አይብላ ብሎ እረገማት በለስ የተባሉ እስራኤላዊያን ናቸዉ፡፡
ማክሰኞ፡-ሻጮች እና ለዋጮችን ከቤተ መቅደስ ባሶጣ ጊዜ ይኼንን በማን ኃይል እንዳደረገዉ የአይሁድ መምህራን ጠይቀዉት ነበር ማቴ 21-23 ስለሆነም የጥያቄ ቀን ይባላል፡፡
ረቡዕ፡-ምክረ አይሁድ ይባላል ምክንያቱም የአይሁድ ሊቃነ ካህናት እና ጸሐፍት ጌታን እንዴት መያዝ እንዳለባቸዉ ምክር ያጠናቀቁበት ቀን በመሆኑ
ሐሙስ፡-በቤተ ክርስቲያን የተለያየ ስያሜዎች ያሏቸዉ በርካታ ድርጊቶች የተፈጸሙበት ነዉ፡፡
  ûጸሎተ ሐሙስ ይባላል፡መድኃኒዓለም ክርስቶስ አይሁድ መጥተዉ እስኪይዙት ድረስ ሲጸልይ ያደረበት ነዉና ጸሎተ ሐሙስ ተባለ
ûሕጽበተ ሐሙስ ይባላል፡-ጌታችን በዚህ ዕለት የደቀ መዛሙርቱን እግር ጎንበስ ብሎ በታላቅ ትህትና አጥቧልና
û የሚስጢር ቀን ይባላል፡-ከሰባቱ ምስጢራት አንዱ የሆነዉን ምስጢረ ቁርባን በዚህ ዕለት ተመስርቷልና
û የሐዲስ ኪዳን ሐሙስ ይባላል፡-ምክንያቱም የ ኦሪት መስዋዕት የሆነዉ ያእንስሳት ደም ማብቃቱን ገልጦ ለድህነተ ዓለም ራሱን የተወደደ መስዋዕት አድርጎ ያቀረበበት ዕለት በመሆኑ
û የነፃነት ሐሙስ ይባላል፡-ምክንያቱም ለኃጢአትናለዲያብሎስ ባርያ መሆኑ ማብቃቱና የሰዉ ልጅ ያጣዉን ክብር መልሶ ማግኘቱ የተረጋገጠበት ቀን ስለሆነ ነዉ፡፡
ዓርብ፡-ጌታችን ከ ጲላጦስ አደባባይ እስከ ሊጦስጥራ የተንገላታበት ለአዳምና ለልጆቹ በምልዕልተ መስቀል ለሞት እራሱን አሳልፎ የሰጠበት ቀን ነዉ፡፡
ቅዳሜ፡-በዚች ዕለት የጌታችን መከራ በማሰብ በጾም ታስባ ስለምትዉል ቅዳም ሥዑር ወይም የተሻረችዉ ቅዳሜ ትባላለች፡፡ካህናቱም ለምዕመናን ለምለም ቄጤማን የሚያድሉበት ዕለት ስለሆነ ለምለም ቅዳሜም ትባላለች፡፡እንደዚሁም ልዑል እግዚአብሔር በዚህ ቀን 22ቱን ስነ ፍጥረታት ፈጥሮ ከስራዉ ያረፈበት ዕለት በመሆኑ ቅ/ቅዳሜ ይባላል፡፡
                                  ዳክርስ
       ፀሐይ ብርሃኗ ነጥፎ የበርባኖስ ክንብንብ ስታጠልቅ
      ጨረቃ በሀዘን ተዉጣ በደም አበላ ስትጠመቅ
     ተፈጥሮ ስርዓቷ ተዛብቶ ቀኑ በጽልመት ሲቀየር
      አለታት በፍርሀት ተንጠዉ በድን አካላቸዉን ሲንሞሱ
      ወዳጅህ ልቡ ተነክቶ አንተን  ለድህነት ሲጠራህ
      ህይወት በቀኝህ ተሰቅሎ የቀለጠ ፍቅሩን ስታይ
      በመጨረሻዋ ደቂቃ ህይወትን መዋጀት ሲገባህ
      ታአምሩን በአይኖችህ እያየህ ቃሉን በጀሮህ እየሰማህ
       ምን የሚሉት ፈሊጥ ነዉ ይኼ በበደል ላይ በደል ማከል
       ልብን ተራራ አሳክሎ አንደበትን ለስድብ ማሾል
      ልብህ ባለማመን እረግረግ በክህደት አረንቋ ተጣለ
      ዋ!ምነዋ! ዳክርስ የእምነት ቋጥህ ሟጠጠ
                              ሰባቱ የመስቀል ላይ ንግግሮች
& ኤሎኼ ኤሎኼ ኤልማስ ላማ ሰበቅታኒ ትርጓሜዉም አምላኬ አምላኬ ለምን ተዉኽኝ
& አባት ሆይ የሚያደርጉትን አያዉቁምና ይቅር በላቸዉ
& አባት ሆይ ነፍሴን በእጅህ አደራ እሰጣለሁ
& ዛሬ በገነት ከእኔ ጋር ትዉላለህ
&ተጠማሁ
& እነሆ ልጅሽ እነኋት እናትህ
& የተጻፈዉ ሁሉ ተፈጸመ
                          ወስብሐት ለእግዚአብሔር

1 comment:

  1. ሙሴም በምድረ በዳ እባብን እንደ ሰቀለ እንዲሁ በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ የሰው ልጅ ይሰቀል ይገባዋል።

    16 በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲሁ ወዶአልና።

    17 ዓለም በልጁ እንዲድን ነው እንጂ፥ በዓለም እንዲፈርድ እግዚአብሔር ወደ ዓለም አልላከውምና።

    18 በእርሱ በሚያምን አይፈረድበትም፤ በማያምን ግን በአንዱ በእግዚአብሔር ልጅ ስም ስላላመነ አሁን ተፈርዶበታል።

    19 ብርሃንም ወደ ዓለም ስለ መጣ ሰዎችም ሥራቸው ክፉ ነበርና ከብርሃን ይልቅ ጨለማን ስለ ወደዱ ፍርዱ ይህ ነው።

    20 ክፉ የሚያደርግ ሁሉ ብርሃንን ይጠላልና፥ ሥራውም እንዳይገለጥ ወደ ብርሃን አይመጣም፤

    21 እውነትን የሚያደርግ ግን ሥራው በእግዚአብሔር ተደርጎ እንደ ሆነ ይገለጥ ዘንድ ወደ ብርሃን ይመጣል።

    ReplyDelete